Thursday, May 9, 2013

ከዋሽንግተንና አካባቢዉ የጋራ ግብረሃይል የተሰጠ መግለጫ


ሚያዝያ 30 ቀን 2005 ዓ/ም
አምባገነኑ እና በፍጹም ማናለብኝነት የኢትዮጵያን ህዝብ ስብእና በመርገጥ፤ በማፈናቀል፤ በመግደል፤ ነጻነቱን በመቀማት፤ ሀገራችንን እየጠፋት የሚገኘዉ የወያኔ ስርአት ከእለት እለት እየፈፀመ ያለዉ ግፍ እየከረረ መጥቷል። ለነጻነታቸዉ ሚታገሉ ዜጎችን በሀገራቸዉ አሸባሪ እያለ እያሰረ ይገኛል። ድምጻችን ይሰማ፤ የእምነት ነጻነት ይጠበቅ፤ ህገ መንግስቱ ይከበር እያሉ የሚታገሉ ወገኖቻችንን አክራሪ እያለ ሲሻዉ በየእስር ቤት ያጉራል፤ አልያም ይደበድባል ወይም ይገድላል። የተከበሩ የእምነት ተቋማትን በኢንቨስትመንት ስም አያጠፋ ይገኛል። የሀገሪቱን መሬት ነዋሪዉን በማፈናቀል ለዉጭ ባለብቶች በዉዳቂ ዋጋና የህብረተሰቡንና ሀገርን ጥቅም በማያስጠብቅ ሁኔታ ሸንሽኖ እየሸጠ ይገኛል። በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ እህቶችችንን በአረብ ሀገራት ከባርነት ባልተናነሰ ሁኔታ እየሸጠ ይገኛል። የሀገሪቱን አንጡራ ሀብት በስርአቱ በሚመሩ ኩባንያዎችና በዙርያቸዉ በተሰበሰቡ ፍርፍሪ ለቃሚዎቻቸዉና አጫፋሪዎቻቸዉ አንጠፍጥፎ በመዝረፍ ላይ ነዉ። የህዝቡን በነጻ የመደራጀትና የመምረጥ መብቱን በመግፈፍ ዲሞክራሲን ሙሉ በሙሉ አጥፍቷል፤ በተጨማሪም ተቃዋሚ ፖለቲካ ድርጅቶችንም የማጥፋት ዘመቻዉን እያጧጧፈ ይገኛል። የሀገራችን ዜጎችም በሚደርስባቸዉ እንግልት፤ ኑሮ ዉድነትና፤ ተስፋ አጥነት በመማረር ከመቹዉም ጊዜ በበለጠ ሁኔታ ሀገራቸዉን በመጣል ወደ ጎረቤት ሀገራት በመሰደድ ለእጅግ ከፍተኛ ስቃይና መከራ በመዳረግ ላይ ይገኛሉ። ይሀ ሁሉ አልበቃ ብሎ በሀገራችን ከዚህ በፊት ታይቶ በማይታወቅ ሁኔታ በፍጹም ዘረኝነት ላይ በተመረኮዘ መርህ የአማራ ተወላጆች የሆኑ ወገኖቻችንን ግልጽ የሆነ የዘር ማጥፋት ወንጀል በመፈጸም ከቀያቸዉ አፈናቅሏል። ባጠቃላይ ዘረኛዉና ሀገር አጥፊዉ የወያኔ ስርአት በሃገራችንና በወገናችን ላይ እየፈጸመ ያለዉን ግፍ ዘርዝሮ ለመግለጽ እጅግ ያዳግታል።
ግፈኛዉ የወያኔ ስርአት በሀገራችን እያደረሰ ያለዉን ግፍና ዘረፋ ሳያበቃ፤ የማይጠረቃ የዘረፋ ቋቱን በመያዝ በተለያዩ የዓለም ክፍሎች ከሚገኙ ኢትዮጵያዉያን ላይ ለዓባይ ግድብ ማሰርያ በሚል ሽፋን ገንዘብ ለመሰብሰብ ጥረት እያደረገ ይገኛል። ነገር ግን የወያኔ ስርአት ባሁኑ ወቅት ያልተረዳዉ አንድ ገሃድ የሆነ አዉነታ አለ። የኸዉም ወቅቱ አብዛኛዉ በዉጭ የሚኖር ሀገር ወዳድ ዜጋ ሁሉ ከመቼዉም ጊዜ በበለጠ ሁኔታ ግፈኛዉ ስርዓት በሚፈጽመዉ ግፍ በመማረር በአንድነት በመቆም ሀገሩንና ወገኑን ከወያኔ የግፍ ቀንበር ለማላቀቅ በቁርጠኝነት በመነሳት እየታገለ ሚገኝበት ጊዜ መሆኑን ነዉ። በመሆኑም ዓባይ ከመገደቡ በፊት ነጻነት፡ በሚል የጋራ መርህ አንድ በመሆን፤ የስርአቱን ህገወጥ የሆነ የገንዘብ ማሰባሰብ ጥረቶች እያከሸፈ ይገኛል። በተከታታይም በሳኡዲ አረቢያ፤ በደቡብ አፍሪካ፤ በኖርዌይ፤ በስዊድን፤ በአሜሪካ የወያኔዉ ዘራፊ ደም መጣጮች ገንዘብ ለመዝረፍ ያረደጉትን ሙከራዎች በማክሸፍ ቅሌት አከናንቦ ወደ መጡበት መልሷቸዋል። በዚህም ሳያበቃ በሀገሩ ህገ ወጥነትን የተካነዉ ስርአት የህግ የበላይነት ባለባቸዉ ሀገሮች ዉስጥ ያለፍቃድ እያከናወነ የሚገኘዉን የቦንድ ሽያጭ ለየሀገራቱ በማሳወቅ የክስ ዘመቻዉን እያጧጧፈዉ ይገኛል። በዚህም የተደናገጠዉ ስርአት ያካሄድ ለዉጥ በማከናወን በቅርቡ እኤአ ሜይ 11 ቀን 2013 ዓ/ም በአሜሪካን ሀገር በኒዉዮርክ ከተማ ህዝቡን ወገኑንና ሀገሩን በመክዳት የግፍ፡ የግድያ፤ የዘረኝነት፤ የዝርፍያና፤ የእስር አምባሳደሩ ለመሆን በመረጠዉ ድምጻዊ ንዋይ ደበበ ዋና አቀንቃኝነት ለማቅረብ ዝግጅቱን አጠናቋል።
ይህን ህዝባችን ቁስል ላይ እንጨት የሚሰነቁር፤ እስካሁን ባደረግነዉ ትግል ላይ ደሞ ያላቸዉን ንቀት የሚያሳይ እኩይ ተግባር እኛ በዋሽንግተን ዲሲና አካባቢና በኒዉ ዮርክ አካባቢ የምንገኝ ኢትዮጵያዉያን አጥብቀን እንቃወመዋለን። በዚህም መሰረት፡
1. በእለቱ ዝግጅቱ በሚከናወንበት ቦታ እጅግ ከፍተኛ የተቃዉሞ ሰልፍ የምናደርግ ስለሆነ ሁሉም ሀገር ወዳድ የሆነ ወገን ሁሉ በመገኘት ሆዳምነትን፤ ባንዳነትንና፤ አድር ባይነትን አጥብቀን ለመቃወም እንድንሰባሰብ ጥሪ እናቀርባለን።
2. ሌሎች በዝግጅቱ ለመሳተፍ የሚያስቡ ካሉም ዉሳኔያቸዉን ከሃገርና ከወገን ደህንነት አኳያ ደግመዉ እንዲያጤኑ ወገናዊ ማሳሰብያችንን እናስተላልፋለን።
3. በእለቱም በዝግጅቱ ላይ የሚሳተፉትን በቪዲዮና በካሜራ በመቅረጽ በተለይ እዚህ አገር የፖለቲካ ጥገኝነት በመጠየቅ ስርአቱን በሚደግፉት ላይ በሌሎች ሀገሮች በህግ እንደ ተጀመረዉ እኛም ማንነታቸዉን በማጣራት ለሚመለከታቸዉ የመንግስት አካላት የምናስተላልፍና ጉዳዩም ዉሳኔ እስኪያገኝ አጥብቀን የምንከታተል መሆኑን እናሳዉቃለን
4. በዚህ ዝግጅት ላይ ተሳታፊ የሚሆኑ አፍቃሪ ወያኔ / ፀረ ህዝብ ድምጻዉያን ላይ ካሁን በሗላ በዓለም ዙርያ በሚያዘጋጇቸዉ ማናቸዉም ዝግጅቶች ላይ ላለመገኘት የጋራ ማእቀብ ጥሪ እናቀርባለን። ይህም በመሆኑ በእለቱ እነማን እንደተሳተፉ በማጣራት ወደፊት ለህዝቡ የምናሳዉቅ ይሆናል።
የወገናችን ሰቆቃ በጋራ እንደሚወገድ ስለምናምን እስካሁን በጋራ ያከናወናቸዉ እጅግ አርኪ ተግባራት ስኬታማ እንዲሆኑ ወገናችን ያደረገዉን ከፍተኛ ተሳትፎ እናደንቃለን። ሃገራችንና ወገናችንን ነጻ የማድረጉ ትግል በድል እስኪጠናቀቅ ድረስ የጀመርነዉን ትግል በጽናት እንድንገፋበት ጥሪያችንን እያቀረብን በኒዉ ዮርክ በሚደረገዉ ሰልፍ ላይ ለመሳተፍ በ dcjointtaskforce@gmail.com በመጻፍ ተጨማሪ ማብራርያ ማግኝት የሚቻል መሆኑን እናሳዉቃለን።
ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር!!!

No comments:

Post a Comment