Wednesday, February 25, 2015

“መረጃ አውጡ፣ የደበቃችሁትን ሁሉ ተናገሩ”


የተቃዋሚ ፓርቲዎች አመራሮች በጨለማ ቤት መታሰራቸውን አስታወቁ

dark



በሽብርተኝነት ተጠርጥረው ማዕከላዊ ፌደራል ወንጀል ምርመራ የሚገኙት የሦስት ተቃዋሚ ፓርቲዎች የቀጠና/ዞን አመራሮች ለ16 ተከታታይ ቀናት በጨለማ ክፍል መታሰራቸውን ለፍርድ ቤት አስታወቁ፡፡
የካቲት 17 ቀን 2007 ዓ.ም በፌደራሉ የመጀመሪያ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ ችሎት የቀረቡት የሰማያዊ (የፓርቲው የጎንደር አደራጅ አቶ አግባው ሰጠኝ)፣ የአንድነት እና መኢአድ የዞን አመራሮች “መረጃ አውጡ፣ የደበቃችሁትን ሁሉ ተናገሩ” እያሉ እንደሚደበድቧቸውና በጨለማ ክፍል እንዳሰሯቸው ተናግረዋል፡፡ ፖሊስ አሁንም መረጃየን ሰብስቤ አልጨረስኩም በሚል ተጨማሪ 8 ቀናት ጠይቆ ተፈቅዶለታል፡፡
ተጠርጣዎቹ በማዕከላዊ እየደረሰባቸው የሚገኘውን ሰቆቃ አስመልክተው ለፍርድ ቤት አቤት ማለታቸውን ተከትሎ ፍርድ ቤቱ ፖሊስ የቀረበበትን አቤቱታ እንዲያስተካክል ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡
ተጠርጣሪዎቹ በጎንደርና ጎጃም አካባቢዎች የዛሬ አራት ወር ገደማ በፖሊስ ታስረው ወደ አዲስ አበባ ማዕከላዊ ፌደራል ወንጀል ምርመራ እንዲዛወሩ የተደረጉ ሲሆን፣ ጠበቃቸው በተደረገባቸው ክልከላ ምክንያት ተጠርጣሪዎቹን ካገኟቸው 2 ወር እንደሞላቸው ተናግረዋል፡፡ ከተጠርጣሪዎቹ መካከል አቶ አግባው ሰጠኝ እየተፈጸመበት ያለውን የመብት ጥሰት በመቃወም የርሃብ አድማ ላይ መሆኑ የታወቀ ሲሆን አድማውን ከጀመረ ሁለተኛ ቀኑ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡
ፍርድ ቤቱ በሰጠው የጊዜ ቀጠሮ መሰረት አመራሮቹ የካቲት 25 ቀን 2007 ዓ.ም ፍርድ ቤት ይቀርባሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡ (ነገረ ኢትዮጵያ ፌስቡክ ገጽ)
http://www.goolgule.com/opposition-party-leaders-under-severe-interrogation-and-torture/

ሳይገባቸው ቻይና በነገራቸው የሚያውቁትን የሚረሱ ማን ያስተምራቸው!


ፕ/ር መስፍን ወልደ-ማርያም

haile china



የጎረቤት ኬንያ ዳኛ ለኬንያ መንግሥት አስፈጻሚው ክፍል ልኩን ነገረው፤ ሕገ መንግሥቱን በመርፌ አስተኝተህ ሕገ መንግሥቱን የሚጻረር ሕግ ለማውጣት አትችልም፤ ስለዚህም የሰነዘርኸውን የጉልበት ሕግ አንሣ፤ አለው፤ ዳኛ አይጥፋ! ሌላ ቢቀር ከጎረቤት ዳኝነትን እንስማ፡፡
ኢትዮጵያ ውስጥ ዳኛ ቢኖር ስንት ጋዜጠኛ፣ ስንት የሃይማኖትና ስንት የፖሊቲካ መሪዎች ከየወህኒ ቤቱ ይወጡ ነበር! ሁላችንም እንደልባችን ሳንፈራ፣ ሳንፈራራ በሙሉ ነጻነት ችግሮቻችንን የወያኔን ጭቆና ጨምሮ ለመወያየትና መፍትሔዎችን ለመለዋወጥ የምንችልበት መድረክ፣ ጋዜጣ፣ መጽሔት፣ ራድዮና ቴሌቪዥን በኢትዮጵያ ውስጥ ይኖረን ነበር፤ ስንት ሰው ሥራ ያገኝ ነበር፡፡
ከሁሉም በላይ በየመንገዱ ጠመንጃ የያዘ ሊያስፈራራን የሚሞክር ሆድአደር እያየን፣ እንደዚሁም በየጫካው ያሉትን እያሰብን ሰላማችንን ከምናጣ አበባውን ትተን፣ ሩዙን ትተን፣ የተወደደልንን ጤፋችንን እያመረትን አዲስ ኑሮ ብንጀምር የተሻለ ነበር፡፡
ግን አንድ እንቅፋት አለብን፤ እነዚህ ከየኪዮስኩ እውቀት ገዝተን አዋቂዎች ሆነናል የሚሉት እንትኖች መጀመሪያ ችግሩ እንዲገባቸው፣ ሁለተኛ መፍትሔው እንዲገባቸው፣ ሦስተኛ ጉልበትና እውቀት አንድ አለመሆናቸውን ብቻ ሳይሆን በጉልበት እውቀት የማይገኝ መሆኑን ማሳመን በረዶ እየወረደ የስሜን ተራራን መውጣት ነው፤ በረዶ ሳይኖር ወጥቼዋለሁ!
እነዚህን የጉልበት አዋቂዎች — ስለሽማግሌዎችና አሮጊቶች ሳያስቡ፣ ስለመብራት ኃይል ሳያስቡ፣ ስለውሀ ሳያስቡ ሁሉም በጉልበት ፎቅ ይውጣ የሚሉ! ይባስ ብለው ለእስረኛውም ፎቅ እየሠሩለት ውጣ! ሊሉት ነው!
እነዚህ የጉልበት አዋቂዎች የአበሻ ኑሮ፣ ቡናው፣ ሙቀጫው፣ ምጣዱ፣ በርበሬው፣ ቁሌቱ፣ ቄጤማው፣ ዶሮና በግ ማረዱ፣ ኧረ ስንቱ! ሳይገባቸው ቻይና በነገራቸው የሚያውቁትን የሚረሱ ማን ያስተምራቸው! እናውቃለን ስለሚሉ እንዴትስ ይማራሉ? በእውነት ለመማር ቢፈልጉስ ስንት ዓመት ሊያስፈልጋቸው ነው!
እግዚአብሔር እነሱንም እኛንም በምሕረቱ ይጎብኘን! የሚያስተምር ጎረቤት አያሳጣን! (ምንጭ: ከፕ/ር መስፍን ፌስቡክ ገጽ)
http://www.goolgule.com/forgetting-what-they-have-learned-and-taught-by-the-chinese/

Thursday, February 19, 2015

20ኛው የዞን9 ጦማርያን እና ጋዜጠኞች የ”ፍርድ ቤት” ውሎ- በገዛ ፍቃዴ ለቅቄያለሁ ያሉት ዳኛ ደግመው ተሰይመዋል!


ለሶስት መቶ ቀናት በእስር ላይ የቆዬት ጦማርያን ለ20ኛ ጊዜ “ፍርድ ቤት” ቀርበዋል፡፡
ትላንትና የካቲት 12 ቀን ገዥው ህወሃት 41ደኛ ልደቱን ባከበረበት በተመሳሳይ ቀን በነሶልያን ሽመልስ የክስ መዝግብ “ፍርድ ቤት” የቀረቡት ጦማርያን እና ጋዜጠኞች የእምነት ክህደት ቃላቸውን ሰጥተዋል፡፡Zone 9 bloggers
“የፍርድ ሂደቱ” ጠዋት ሊጀመር ተቀጥሮ የነበረ ቢሆንም ያለቅጥ ዘግይተው የተሰየሙት ዳኞች ተከሳሾቹ ለከሰአት ስምንት ሰአት ለሚጀምረው ችሎት አንዲገኙ ለከሰአት ተቀጥረው ነበር፡፡ ከሰአት ስምንት ሰአት ላይ ችሎቱ ከመጀመሩ በፌት ባሉት ሰአታት ልደታ ፍርድ ቤት ጊዜያቸውን ያሳለፉት ጦማርያን ከሰአት በኋላ “ፍርድ ቤት” ቀርበዋል፡፡ ችሎቱ ላይ ባለፈው ቀጠሮ አቤቱታ ቀርቦባቸው አቤቱታውን “ፍርድ ቤቱ” ባይቀበለውም በገዛ ፍቃዴ ከችሎቱ ለቅቄያለሁ ያሉት ዳኛ ሸለመ በቀለ መልሰው ችሎቱን ሰብስበዋል ፡፡ ከችሎቱ ለመነሳታቸውም ሆነ ላለመነሳታቸው የተሰጠ ማብራሪያ ሳይኖር ከሁለተኛ ተከሳሽ ከጦማሪ በፍቃዱ ሃይሉ ጀምሮ እያንዳንዳቸው ተከሳሾች በስም እየተጠሩ የተጠረጠሩበትን ወንጀልመፈጸም እና አለመፈጸማቸውን ቃል አንዲሰጡ የተጠየቁት ጦማርያን እና ጋዜጠኞች ሲመልሱ
በፍቃዱ ሃይሉ – እኔ ክሱን ከአምስት ጊዜ በላይ በተደጋጋሚ አንብቤዋለሁ ምንም የሚገባ ነገር አላገኘሁበትም ሲል ዳኛው አቋርጠውት አሁን ምንም አይነት ዝርዝር ውስጥ አልገባም በማለታቸው “የሽብር ወንጀል ለመፈጸም አላሰብኩም አልፈጸምኩት አልፈጽምም ሽብር ተፈጽሞብኛል” ሲል መልሷል፡፡ ከበፍቃዱ በማስከተል ቃሉን የሰጠው ጦማሪ ናትናኤል “ህግ የሚከበርበት አገር ቢሆን ኖሮ ዛሬ እዚህ ቦታ መቆም የነበረባቸው አሳሪዎቼ ናቸው ፣ ምንም ወንጀል አልፈጸምኩም “ያለ ሲሆን ጦማሪ አጥናፍ “ወንጀል አልፈጸምኩም” ፣ ጦማሪት ማህሌት “ምንም አይነት ወንጀል አልፈጸምኩም” ብላ ቃሏን ስትሰጥ ጦማሪ አቤል በበኩሉ “ክሱ ግልጽ አይደለም” ሲል ዳኛው ምንም አይነት ተጨማሪ ነገር ሳያስፈልግ ቀጥታ ቃል እንዲሰጥ ማሰጠንቀቂያ ሰጥተዋል፡፡ በመሆኑም አቤል “የህብረተሰቡን ደህንነት አደጋ ላይ የሚጥል ምንም አይነት የሽብር ተግባር አልፈጸምኩም አላሴርኩም” ሲል በቀጥታ ክሱ ላይ የተጠቀሰውን አንቀጽ ጠቅሶ ቃሉን ሰጥቷል፡፡ ጦማሪ ዘላለም በበኩሉ የተከሰሰበት ወንጀል አንዲብራራለት የጠየቀ ሲሆነ “ፍርድ ቤቱ” ወደኋላ አንመለስም የሚል ማስፈራሩያ በማሰማት በቀጥታ ቃሉን እንዲሰጥ ሲነገረው “የተከሰስኩበት ክስ ግልጽ ባልሆነበት ሁኔታ የእምነት ክህደት ቃሌን መስጠት አልችልም” በማለት በመናገሩ ቃሉን ሳይሰጥ ቀርቷል ፡፡ በህጉ መሰረትም ጥፋተኛ አይደለሁም አንዳለ ተቆጥሮ ተመዝግቧል፡፡
ጋዜጠኛ ኤዶም ካሳዬ -” ምንም ወንጀል አልፈጸምኩም እኔ ነጻ ሰው ነኝ ” ስትል ጋዜጠኛ አስማመው “ወንጀል አልፈጸምኩም” ጋዜጠኛ ተስፋለም ደግሞ “እኔ ጋዜጠኛ ነኝ ጋዜጠኝነት ወንጀል አይደለም እኔ ምንም ወንጀል አልፈጸምኩም” ብሏል፡።
የእምነት ክህደት ቃል መስጠቱነ ተከትሎ አቃቤ ህግ ምስክሮቸን ለመስማት ተለዋጭ ቀጠሮ ይሰጠኝ ብሎ በጠየቀው መሰረት ከአርባ ቀን በኋላ ለመጋቢት 21-23 ለሶስት ቀናት የሰውና የሰነድ ማስረጃ ለማቅረብ ቀጠሮ ተሰጥቷል፡፡ የተከሳሾች ጠበቆች በበኩላቸው አለ የተባለው የሲዲ ማስረጃ ግልባጭ ስላልተሰጠን አንዲሰጠን ብለው የጠየቁ ሲሆን “ፍርድ ቤቱ” እንዲሰጣቸው ትእዛዝ ሰጥቷል፡፡
የተከሳሾች አያያዝ
ባለፈው ችሎት ወቅት ጦማሪ አቤል ዋበላ ያቀረበውን አቤቱታ ተከትሎ ማረሚያ ቤቱ መልስ አንዲሰጥ መጠየቁ የሚታወስ ሲሆን የጦማሪው ጠበቃ ተከሳሹ ከማረሚያ ቤት አስተዳደሩ ጋር በመነጋገር ችግሩን ስለፈቱት አቤቱታውን መቅረቱን ለ”ፍርድ ቤቱ” ተናግረዋል፡፡ ጦማሪ አቤልም በበኩሉ ተጨማሪ የመብት ጥሰት አስካልደረሰብኝ ድረስ ባለፈውን አቤቱታዬን ትቼዋለሁ ያለ ሲሆን ባለፈው ተቀምቶ የነበረው የጆሮ ማዳመጫ መሳሪያም ተመልሶለታል ፡፡ ነገር ግን የሴት ተከሳሾች አያያዝ አንደአዲስ አስቸጋሪ እንደሆነ የሚያያቸው ሰው ገደብ እንዳልተነሳ እና አሁንም በጥቂት ሰዎች ብቻ አንደሚጠየቁ ለፍርድ ቤቱ አቤቱታ በማቅረባቸው የእነሱን አያያዝ አስመልክቶ ማረሚያ ቤቱ መልስ አንዲሰጥ ለመጋቢት 18 ጠዋት ቀጠሮ ተሰጥቶ ችሎቱ ተጠናቋል ፡፡
የዞን9 ማስታወሻ
ሶስት መቶ ቀን እስር እና ከሃያ ቀጠሮ በኋላ የተጀመረው ይህ መደበኛ “የፍርድ ሂደት” እንደተለመደው መጓተቱ ሳያንስ በአንድ ወር በላይ የሚፈጅ ቀጠሮ መሰጠቱ ለክሱ ፓለቲካዊነት አንዱ መገለጫ እንደሆነ እናምናለን፡፡ ሶስት ወር በፈጀ ምርመራ ሂደት ውስጥ ተገኙ የተባሉትን ማስረጃዎች ለማቅረብ የ40 ቀን መዘጋጃ ጊዜ አንደማያስፈልግ ለማንም ሰው በግልጽ የሚታይ ሃቅ ነው ፡፡ በመሆኑም ባለፈው የቀረበው አቤቱታ ላይ አንደተገለጸው ዳኛውም ሆነ የፍትህ ስርአቱ አላግባብ መታሰራችን እና መከሰሳችን ሳያንስ አንድን “የፍርድ ሂደት” በማራዘም አፋጣኝ ፍትህ የማግኘት መብት መቀለጃ እየሆነ አንደሆነ እያሳዬን ነው፡፡ የዞን9 ነዋሪያንና አንባቢዎችም ይህ ፍትህ ስርአቱ ስም የሚደረግ ቀልድ አንደማይጠፋቸው አናምናለን ፡፡
የዞን9 ጦማርያን እና ወዳጅ ጋዜጠኞች በመልካም ጤንነት በጠንካራ ስነልቦና እና በራስ መተማመን ስርአቱን ፌትለፌት እየተገዳደሩ ያሉ ኩሩ ልበ ሙሉ ወጣት ዜጎች ናቸው ፡፡ የተለየ ሃሳብን በሚያራምዱ ጥቂት ወጣቶች የተሸበረውን መንግሰት የምናፍርበት ያህል በጓደኞቻችን አንኮራለን ፡፡
የዞን9 ኩራት ጦማሪ በፍቃዱ ሃይሉ በድጋሚ መልካም ልደት
ስለሚያገባን እንጦምራለን ፡፡
ዞን9
http://ecadforum.com/Amharic/archives/14450/

የ2007ቱን ሀገራዊ ምርጫ ሂደት እና ከምርጫዉ ዉጭ ያሉ አዋጭ አማራጮችን በተመለከተ የአርበኞች ግንቦት 7: የአንድነትና ዲሞክራሲ ንቅናቄ የአቋም መግለጫ


  • Share
    አርበኞች ግንቦት 7: የአንድነትና ዲሞክራሲ ንቅናቄ፣ የኢትዮጵያ ሕዝብ በሰላማዊ፣ ተዓማኒና ፍትሀዊ በሆነ ምርጫ የማይፈልጋቸውን መሪዎች መሻር፤ የሚፈልጋቸውን ደግሞ መሾም የሚያስችሉትን መሠረቶች ለመጣል የሚታገል ንቅናቄ ነው። እንደሚታወቀው የሕዝብ እውነተኛ ፍላጎት የሚገለጽበት እውነተኛ ምርጫ እንዲኖር ገለልተኛና ቀልጣፋ የፍትህ ሥርዓት፣ የጦርና የፓሊስ ሠራዊት ሊኖሩ ይገባል። ነፃ የሚዲያ ተቋማትና በነፃነት የሚንቀሳቀሱ የሲቪክ ማኅበራት መኖርም መታለፍ የሌለባቸው አቢይ ጉዳዮች ናቸው። አማራጭ ፓሊሲዎችን ማቅረብ የሚችሉ በነፃነት የሚንቀሳቀሱ የፓለቲካ ፓርቲዎች ከሌሉም አማራጮች የሉምና ምርጫ ትርጉም የለውም። ይህ ሁሉ ቢሟላ እንኳን ምርጫውን የሚያስፈጽመው አካል ገለልተኛ፣ ሀቀኛና ተዓማኒ ካልሆነ የሚደረገው ምርጫ የመራጩን ሕዝብ ፍላጎት የሚያንፀባርቅ ሊሆን አይችልም።
g 7ከላይ የተዘረዘሩትን የምርጫ እሴቶች ሙሉ በሙሉ ባይሆንም እንኳን የተወሰኑትን በመጠኑም ቢሆን ያካተተ ምርጫ እንዲኖር መጣርና በሂደት የምርጫውን አፈፃፀም ማሻሻል ይቻል ይሆናል በሚል እምነት የዲሞክራሲ ኃይሎች በህወሓት የሴራ ምርጫዎች ሲሳተፉ ቆይተዋል። ሆኖም በህወሓትና በእውነተኛ ምርጫ መካከል  ያለው ተቃርኖ እያደር እየሰፋ ሲሄድ እንጂ ሲጠብ አልታየም።  በህወሓት ሙሉ ቁጥጥር ስር በሚካሄድ ምርጫ ኢትዮጵያን የሚጠቅም ለውጥ ሊመጣ ይችላል የሚለው እምነት ለአርበኞች ግንቦት 7 ፈጽሞ የተሟጠጠው ከምርጫ 97 ማግስት ጀምሮ  ነው። በግንቦት 7 ቀን 1997 ዓም የኢትዮጵያ ሕዝብ በታላቅ የለውጥ ተስፋ የሰጠው ድምጽ በህወሓት የተዘረፈው ከላይ የተዘረዘሩት ተቋማት ያልነበሩ በመሆናቸው፤ ስለዚህም ከምርጫ በፊት ተቋማቱን መገንባት፤ ተቋማቱን ለመገንባት ደግሞ ህወሓትን ከስልጣን ማስወገድ ይገባል ብሎ በማመኑ ነው አርበኞች ግንቦት 7 በሁለገብ የትግል ስልት በመንቀሳቀስ ላይ የሚገኘው።
ያም ሆኖ ግን በምርጫ ላይ ያላቸው ተስፋ ፈጽሞ ያልተሟጠጠ ፓርቲዎችን በማክበርና ሥራቸውንም አስቸጋሪ ላለማድረግ ሲባል ከምርጫ 97 ወዲህ የነበሩ ብሄራዊም ሆነ ክልላዊ ምርጫዎችን አስመልክቶ የኢትዮጵያ ሕዝብ ከምርጫ ዉጭ ያሉ ሌሎች አማራጮችን ብቻ እንዲመለከት አርበኞች ግንቦት 7 ጥሪ አድርጎ አያውቅም ነበር። አሁን ግን የአገራችን ኢትዮጵያ የፓለቲካ ሁኔታዎች  ይህንን የቆየ አቋም በሚያስቀይር መንገድ፤ የአገራችንን የወደፊት ዕድል ብቻ ሳይሆን ባጠቃላይ ያካባቢውን ሰላም በሚጎዳ መልኩ ተቀይሯል። የሰሞኑ የወያኔ እርምጃዎች ትንሽ ተስፋ ያደርግ የነበረውን የዴሞክራሲ ወገንተኛ ተስፋም እምሽክ አድርጎ በልቶታል:: እየተቃረበ ያለው ዓይነት የፌዝ ምርጫ ወያኔ እንደ እንጄራ የራበውን የተቀባይነት እጦት ለአጭር ጊዜ ያስታግስለት ይሆናል እንጂ የሀገሪቱን እያደር እየተወሳሰበ የመጣ ችግር ለጊዜውም እንኳን የሚያስታግስ አይሆንም፤ ይልቁንም ጊዜው በገፋ ቁጥር ችግሩ መቋጠሪያ የጠፋው እየሆነ ይሄዳል::
የሁኔታውን አሳሳቢነት ከግምት ውስጥ በማስገባት የአርበኞች ግንቦት 7: የአንድነትና ለዲሞክራሲ ንቅናቄ አመራር የወቅቱን የአገራችን የፓለቲካ ሁኔታ በጥንቃቄ መርምሮ የሚከተሉት ግንዛቤዎች ላይ ደርሷል።
  1. ህወሓት ብዙዎች እትዮጵያዊያን የተሰውላቸውን አንድነት ፓርቲንና መኢአድን በመበተን የድርጅቶቹን ስምና ንብረት ለአገልጋዮቹ መስጠቱ፤ ከዚህ በፊት ሲያደርግ እንደነበረው የመራጭን ድምጽ መስረቅ ሳይበቃው የምርጫ ተወዳዳሪንም መዝረፍ መጀመሩን አመላካች ነው። ይህ ተግባር ህወሓት የምርጫ ውጤትን ብቻ ሳይሆን ተወዳዳሪዎችንም እሱ ራሱ ለመምረጥ መወሰኑን ያሳያል፤ ከዚህ በተጨማሪ የሴራ ምርጫውን ከጅምሩ ጀምሮ አስቀድሞ እስከተወሰነለት መዳረሻው ድረስ ለምንም ዓይነት ያልተጠበቀ አጋጣሚ (በምርጫው ወቅት የሚደረጉትን ክርክር ተብዬዎች ጨምሮ) እድል ላለመስጠት ወስኖ እየተንቀሳቀሰ መሆኑን በግልጽ ያሳያል፤
  2. ይህ እኩይ ውሳኔ በምርጫ ቦርድ ፊርማና አንደበት ቢነገርም ምንጩ የህወሓት ፓሊት ቢሮ  መሆኑን የሚከተሉት ተግባራት ይጠቁማሉ፤
2.1.         በምርጫ ቦርድ በኩል እንዲገለጽ የተወሰነው እርምጃ ለማስመሰል ያክልም ቢሆን የህጋዊነት ሽፋን እንዲኖረው አለመደረጉ ውሳኔው ፍጹም እብሪተኛ በሆነ አካል መወሰኑን ያመለክታል። እንዲህ                   ዓይነቱ እብሪተኛ አካል ደግሞ የህወሓት ፓሊት ቢሮ ነው። ውሳኔውን ለማስፈፀም የነበረው ጥድፊያም ይህንኑ ያጠናክራል።
2.2.        ለማስመሰያ ያክል እንኳን ምንም አይነት የፍርድ ቤት ትዕዛዝ ሳይኖር ፓሊስ የአንድነትና የመኢአድ ቢሮዎችን መውረሩ፤ ህወሓት አንድነትንና መኢአድን አጥፍቶ የድርጅቶቹን ስሞችና ንብረቶች                   ለሚፈልጋቸው ሰዎች ሰጥቶ በአስቸኳይ ለምርጫ ድራማው በፊት መስመር ሊያሰልፋቸው መወሰኑን አመላካች ነው። እንዲህ ዓይነት ከባድ ውሳኔ የሚሰጠው ደግሞ የህወሓት ፓሊት ቢሮ ብቻ                    ነው።
2.3.        ወደ ፈቃድ መንጠቅ ከመደረሱ በፊትም በሰማያዊ ፓርቲ፣ በአንድነትና በመኢአድ አባላት የደረሰው አረመኔያዊ ድብደባ፤ ንቁ የፓለቲካ ተሳትፎ የሚያደርጉ ዜጎች ላይ የሚደርሰው እስር፣ መሰወርና                 እና ባልታወቁ ሰዎች ተገድሎ መገኘት መብዛት እነዚህን አገራዊ ፓርቲዎች የመበተን የፓለቲካ ውሳኔ መሰጠቱን አመላካቾች ናቸው።
  1. ለጊዜው የፈቃድ ነጠቃና የንብረት ዘረፋ የተፈፀመው በአንድነትና በመኢአድ ላይ ቢሆንም በሰማያዊ ፓርቲ ላይ በየእለቱ እየጠነከረ የመጣው የአፈና እርምጃም በተመሳሳይ ፓርቲውን ወደማገድ አለዚያም ፈጽሞ መንቀሳቀስ ወደማይችልበት ደረጃ ሊያደርሰው ይችላል የሚል እምነት አሳድሯል። ሌሎች ፓርቲዎችም ከዚህ ህወሓት ካሰመረው የውሸት ጫወታ መስመር የመውጣት ዝንባሌ ቢያሳዩ ተመሳሳይ እርምጃ አይቀርላቸውም።
  2. የህወሓት የወቅቱ የጥፋት ዒላማ ያነጣጠረው አንፃራዊ በሆነ መንገድ የተሻለ መዋቅርና ማኅበራዊ መሠረት ባላቸው እና በአገራዊ አጀንዳዎቻቸው በሚታወቁ ፓርቲዎች ላይ መሆኑ፤ የወቅቱ የጥፋት ዘመቻ የኢትዮጵያ አንድነትን የማዳከምና ከፋፍሎ የመግዛት የህወሓት ትልቁ አጀንዳ አካል መሆኑን ያሳያል።
  3. እራሱን በዘር ያደራጀዉና ኢትዮጰያ ዉስጥ ያለዉ ፖለቲካዊና ማኅበራዊ አደረጃጀት ከዚሁ እሱ ከተደራጀበት የዘር አደረጃጀት ዉጭ እንዲሆን በፍጹም የማይፈቅደዉ የወያኔ አገዛዝ፤ መጣፊያው ሲያጥረውና ወደ ማይቀረው ውድቀቱ ሲያመራ፤ እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል እንዳለችው አህያ አገራችን ኢትዮጵያን በቀላሉ ወደማትወጣዉ የዘዉግ ግጭት ዉስጥ አስገብቶ ዘመናት ያስቆጠረዉ አንድነቷ እንዲፈረስ በትጋት እየሠራ መሆኑን ያሳያል።
  4. ከመለስ ዜናዊ ሞት ወዲህ ህወሓት ከሁሉን ጠቅላይ (totalitarian) አገዛዝ ወደ ፋሽስታዊ ቡድንነት ያሽቆለቆለ መሆኑን አርበኞች ግንቦት 7 ተገንዝቧል። ህወሓት ዘረኛ፣ ጠቅላይና ፈላጭ ቆራጭ ጨቌኝ በመሆኑ ፋሽስት ብለነዋል።  ሆኖም በታሪክ የሚታወቁ ፋሺስታዊ አገዛዞች ከፍተኛ ብሄራዊ ስሜት የነበራቸው ሲሆን የህወሓት ፋሽስታዊ አገዛዝ ግን ብሔራው ስሜት አልባ መሆኑ ልዩ እና የበለጠ አደገኛ ያደርገዋል። ይህ ፋሽስታዊ ቡድን የህወሓት መሪዎችንና ጥቂት ሌሎች አጫፋሪዎቻቸውን የያዘ ለጊዜው አስተባባሪ መሪ የሌለው ሆኖም ግን የጦር ሠራዊትን፣ የስለላ መዋቅሩንና ፓሊስን ተቆጣጥሮ በአሁኑ ሰዓት ኢትዮጵያን እየገዛ ያለው ይህ አስኳል የለሽ ፋሽስታዊ ቡድን መሆኑ እጅግ አሳሳቢ ጉዳይ መሆኑን አርበኞች ግንቦት 7 ተገንዝቧል። ይህ ፋሽስታዊ ቡድን ተደላድሎ መሪ እንዲፈጥር ከተፈቀደለት አገራችንን የከፋ መከራ ውስጥ ሊከታት እንደሚችል ግንዛቤ ተወስዷል።

ከላይ በአጭሩ ከተራ ቁጥ 1 እስከ 6 የተዘረዘሩትን በማገናዘብ በግንቦት 2007 ሊደረግ የታቀደውን አምስተኛው ዙር ሀገር አቀፍ የሴራ ምርጫን በተመለከተ የአርበኞች ግንቦት 7 አመራር ውሳኔዎችን አስተላልፎ ከዚህ የሚከተሉት ጥሪዎችን ለኢትዮጵያ ሕዝብ አቅርቧል።
  1. በምርጫ 2007 መሳተፍ ለዲሞክራሲያዊ ለውጥ ሁኔታዎችን ከማመቻቸት ይልቅ ፋሽስታዊውን ቡድን የሚያጠናክርና የኢትዮጵያን ሕዝብ የወደፊት ዕድል የሚገድል በመሆኑ፣ ለፍትህ፣ ለነፃነት፤ ለዲሞክራሲና ለአገር አንድነት ግድ ያላቸው ወገኖች ሁሉ ከአሁኑ ከዚህ የይስሙላ ምርጫ ዉጭ ዓይኖቻቸውንና ሙሉ ጉልበታቸዉን በሌሎች የኢትዮጵያን ሕዝብ ነፃነት በሚያፋጥኑ አማራጮች ላይ እንዲያሳርፉ ጥሪ ያደርጋል። አርበኞች ግንቦት 7 የኢትዮጵያ ሕዝብ ከዚህ ዓይን ያወጣ የሴራ ምርጫ ይልቅ መብቱን፤ ነፃነቱንና እኩልነቱን በሚያፋጥኑለት በሕዝባዊ እምቢተኝነትና በሕዝባዊ አመፅ የትግል አመራጮች ላይ እንዲሳትፍ ለመላው ያገሪቱ ሕዝብ ጥሪ ያስተላልፋል።  ህወሓት ማኅበረሰባችንን ለመከፋፈልና ለማባላት የሚያደርገውን እኩይ ሴራ በጋራ እንድናከሽፈው ወገናዊ ጥሪ ያስተላልፋል፤ “አንከፋፈልም፤ ተከፋፍለንም አንጠቃም“ እንበል ይላል::
  2. ህወሓትን ማስወገድ የሚቻለው በሕዝባዊ እምቢተኝነትና በሕዝባዊ አመጽ በመሆኑ፤  ከሁለቱ አንዱንም አለመያዝ ሌላ ሰው ታግሎ ነፃነቴን ያቀዳጀኝ እንደማለት የሚቆጠር በመሆኑ፤ እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ በአፋጣኝ ከእነዚህ ሁለት የትግል ዘርፎች ዉስጥ የተሻለ አስተዋጽኦ አበረክታለሁ በሚለው የትግል ዘርፍ ውስጥ ተሳትፎ  እንዲያደርግ ጥሪ ያቀርባል።
  3. አርበኞች ግንቦት 7፣ በሁለቱም የትግል ዘርፎች ድርጅታዊ መዋቅሩን እያሰፋና ከሌሎች ድርጅቶች ጋር በመተባበር በሕዝባዊ እምቢተኝነትና በሕዝባዊ አመጽ ህወሓትን ከስልጣን ለማስወገድ አቅዶ በመንቀሳቀስ ላይ የሚገኝ በመሆኑ ኢትዮጵያዊያን በስፋት እንዲቀላቀሉት፤ በኅብረት እንድንቆም እና የህወሓትን ውድቀትና የኢትዮጵያን ትንሳኤ እንድናፋጥን ጥሪ ያደርጋል::
  4. ያለንን አቅም በሙሉ ህወሓትን በማስወገድ ላይ ካዋልነው አንድ ጠንክር ያለ ሕዝባዊ አመጽ አገዛዙን ሊያፍረክርክው የሚችል በመሆኑ፤ በአንድ ወይም በሌላ መንገድ ከምርጫ ጋር ለተያያዙ ሥራዎች ሊውል ታስቦ የነበረው የሰው ኃይል፣ ጊዜ፣ ገንዘብና እውቀት ለሕዝባዊ አብዮት መቀስቀሻነት እንዲውል ጥሪ ያደርጋል።
  5. በውጭ አገራት የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ወገኖቻችንም በ2007 ምርጫ ላይ ጊዜና ንብረት ከማባከን ይልቅ በአንድ ልብ በኢትዮጵያ ውስጥ ለሕዝባዊ አብዮት መቀስቀስ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ እንዲያደርጉ ጥሪ ያደርጋል።   ከሁሉም ዴሞክራሲያዊ ኃይሎች የተውጣጣ አካል የዚህን ጥሪ ተፈፃሚነት እንዲከታተል ቢደረግ ይበልጥ ውጤታማ ይሆናል ብሎ ያምናል።

http://www.zehabesha.com/amharic/archives/39133

Sunday, February 8, 2015

ልደቱ አያሌው በቀጣዩ “ምርጫ” አልወዳደርም አሉ – “ካለፉት ምርጫዎች የተለየ ምንም ነገር አይመጣም” ሲሉ ምርጫውን አጣጣሉት

lidetu ayalew
“ቴአትረ ቦለቲካ” የሚል መፅሃፍ ሊያወጡ ነው
በመጪው ግንቦት በሚካሄደው አገራዊ ምርጫ ካለፈው ምርጫ የተለየ ውጤት ቨመጣል ብለው እንደማይጠብቁ የተናገሩት የቀድሞው የኢዴፓ ፕሬዚዳንት አቶ ልደቱ አያሌው፤ በምርጫውም እንደማይወዳደሩ አስታወቁ፡፡ በ “ቴአትረ ቦፖለቲካ ፣ አሉባልታና የአገራችን ፖለቲካ ገመና” በሚል ርዕስ የፃፉት አዲስ መፅሀፍ በቅርቡ በገበያ ላይ እንደሚውልም ተናግረዋል፡፡
“የኢህአዴግን አካሄድና የተቃዋሚው ጎራ ያለበትን ሁኔታ ሳየው በግንቦቱ ምርጫ ካለፈው የተለየ ነገር ይመጣል ብዬ አላስብም” ያሉት አቶ ልደቱ፤ ኢህአዴግ ምርጫውን ሙሉ በሙሉ በራሱ ቁጥጥር ስር አድርጎ እንደቀጠለ ነው፣ ተቃዋሚው ጎራም ካለፉት ስህተቶቹና ድክመቶቹ ተምሮ ራሱን ለማሻሻል ያደረገው ብዙ ነገር የለም ሲሉ ምክንያታቸውን ገልፀዋል፡፡ “ድፍረት አይሁንብኝ እንጂ ተቃዋሚው ጎራ በፓርላማ ያለችውን አንድ መቀመጫ አስጠብቆ ይቀጥላል ወይ የሚለው በራሱ ለኔ ጥያቄ ነው” ሲሉም ጥርጣሬያቸውን አስቀምጠዋል፡፡
በተቃዋሚ ፓርቲ ዙሪያ የተደረጉ የትብብር ሙከራዎች ትግሉን የጎዱ እንጂ የጠቀሙ አይደሉም ሲሉ የሚሞግቱት አቶ ልደቱ፤ ፓርቲዎች በእንተባበር ጥያቄዎች ባይዳከሙ ኖሮ በአሁኑ ወቅት ሁለት ወይም ሶስት ጠንካራ ፓርቲዎች ይኖሩን ነበር ብለዋል፡፡
“ቴአትረ ቦለቲካ፡ አሉባልታና የአገራችን ፖለቲካ ገመና” የተሰኘ ሶስተኛ መፅሃፋቸው በቅርቡ እንደሚወጣ የጠቆሙት አቶ ልደቱ፤ መፅሃፉ በኢትዮጵያ ፖለቲካ አሉባልታዎች ዙሪያ እንደሚያጠነጥን ተናግረዋል፡፡ አሉባልታ የተቃውሞ ጎራውን ትግል ክፉኛ እንደጎዳውም ከአዲስ አድማስ ጋር ባደረጉት ቃለምልልስ ገልጸዋል፡፡
- See more at: http://www.zehabesha.com/amharic/archives/38800#sthash.dwCFcPry.dpuf