Thursday, May 16, 2013

ወደ ቤንሻንጉል ጉሙዝ እንዲመለሱ የተደረጉት የአማራ ተፈናቃዮች አለመረጋጋታቸውን ተናገሩ


ግንቦት ፰ (ስምንት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-ባለፈው ሚያዝያ ከቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ከተፈናቀሉ በኋላ በድርድር ወደ ተፈናቀሉበት ቤንሻንጉል ጉሙዝ  እንዲመለሱ የተደረጉት የአማራ  ተወላጆች ዳግም የመፈናቀል ስጋት አንዣቦብናል አሉ፡፡
የት ተወልድን እንዳደግን፣ የቀድሞ ሠፈራችንና ቀበሌያችንን በመመዝገብ ሂደት ላይ ያለው የዞኑ አስተዳድር ሚስጥራዊና ድብቅ የማፈናቀል ዘመቻውን ሊቀጥል እንደሚችል በተወሰነ መልኩ መገንዘብ ችለናል ያሉት ስማቸው እንዳይገለፅ የፈለጉ አንድ የሴባ ቀበሌ ኗሪ በሁኔታው ሁሉም ግራ መጋባት ላይ እንዳለ ተናግረዋል፡
እርሻ እንዳናርስ መሬት ተከልክለን፣ በበሽታ፣በርሀብና በችግር እየተሠቃየን ኑሮ ብለነው አለን የሚሉት እኒህ ግለሠብ ወደ ቦታው ከመመለስ ወጭ ምንም ዓይነት ትርጉም ያለው መንግስታዊ ትብብርና ድጋፍ እንዳልተደረገላቸው ጨምረው ገልፀዋል፡፡
ከዚህ ጋር በተያያዘ በማይታወቅ ጉዳይ የአማራ ብሔር ተወላጆች ላይ የእስራት እርምጃ እየተወሠደ ሲሆን እስከ አሁን ከስድስት በላይ ዜጎች ለእስር እንደተዳረጉ አንድ ሌላ ስማቸው እንዳይገለፅ የፈለጉ የሴባ ቀበሌ ኗሪ የሆኑ የኦሮሞ ብሔር ተወላጅ ተናግረዋል፡፡
ልጄ አማራ ነች የሚሉት እኒህ ግለሰብ ነገ በልጄ ላይ ሊወሰድ የሚችለውን ግፍ ማጋለጥ ይኖርብኛል በማለት  አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።
ኢሳት ጉዳዩን በማስመልከት ለአካባቢው ተወፈናቃዮች ተወካይ ከሆኑት ግለሰቦች  ጋር ቃለምልልስ አድርጓል። ግለሰቡ የመንግስት ባለስልጣናት 5 በመቶ የማይሞሉ ሰዎችን ሀብት ለማስመለስ ጥረት ቢያደርጉም፣ ከ95 በመቶ በላይ የሚሆነው ሀብትና ንብረቱ እንዳልተመለሰለት፣ በገጠር ነዋሪ የሆነው ህዝብ ስራ አለመጀመሩንና በአካባባው የሚሰማው ዛቻ ተመሳሳይ መፈናቀል ይከሰታል በሚል ህዝቡን ስጋት ላይ እንደጣለው ተናግረዋል።
ሌላው ተመላሽ ተፈናቃይ እንዲሁ በአካባቢው የሚሰማው ዛቻ ስራቸውን ተረጋግተው ለመስራት እንዳላስቻላቸው ተናግረዋል
በተመሳሳይ ዜናም የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት ( መኢአድ) እንዲሁም የአለማቀፉ የህግ ምሁር ዶ/ር ያእቆብ ሀይለማርያም በተፈናቃይ የአማራ ተወላጆች ላይ የደረሰውን የሰብአዊ መብት ጥሰት በተመለከተ በመኢአድ ጽህፈት ቤት  ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል።
የመኢአድ ፕሬዚዳንት ኢ/ር ሀይሉ ሻውል በሰጡት መግለጫ የኢህአዴግ መንግስት ስልጣን ከያዘ ጀምሮ የአማራውን ህዝብ በተለያዩ ዘዴዎች በድብቅ እና በግልጽ ሲያፈናቅል መቆየቱን አስታውሰው፣  አሁንም በቤንሻንጉል ጉሙዝ እና በደቡብ ክልል በቤንቺ ማጂ ዞን አካባቢዎች የሚካሄደው መንግስታዊ የማፈናቀልነ ዘመቻ አለመቆሙን ተናግረዋል።

በሚያዚያ ወር ማፈናቀሉ ቀጥሎ የሶስት ወር እድሜ ያላቸውን ህጻናትና ሴቶች ጨምሮ 90 አባዎራዎች  ሆነ ተብሎ እንዲፈናቀሉ ተደርገዋል ሲሉ ኢንጂነር ሀይሉ ተናግረዋል።
ጉዳዩን እስከ አለማቀፍ ፍርድ ቤት እንደሚያደርሱት የተናገሩት ኦንጂነሩ ፣ በኢትዮጵያ በከፍተኛው ፍርድ ቤት ክስ ለማቅረብ ዝግጅታቸውን ማጠናቀቃቸውንና  ለዚህም አለማቀፉ ምሁር ዶ/ር ያእቆብ ከጎናችን እንደቆሙ ገልጸዋል።
ዶ/ር የእቆብ በበኩላቸው፣  ከአርባ ጉጉ ጀምሮ በአማርኛ ቋንቋ ተናጋሪዎች ላይ ሳይሆን በአማራ ህዝብ ላይ እየደረሰ ያለው በደል እና ደባ ከፍተኛ መሆኑን ጠቁመው ነገር ግን የዘር ማጥፋት ነው ለማለት ባያደርስም ዘር የማጥራት ወንጀል መፈጸሙንና እስከ አለማቀፍ ፍርድ ቤት ደርሶ ሊያስከስስ የሚችል ድርጊት መሆኑንና ይህን ክስ ለመመስረትም መረጃው እንዳላቸው ተናግረዋል።
ጠቅላይ ሚ/ር  ሀይለማርያም ደሳለኝ በፓርላማ ያደረጉት ንግግር በቆ ማስረጃ መሆኑን ዶ/ር ያእቆብ አክለው ተናግረዋል።
ዶ/ር ያእቆብ  በከፍተኛው ፍርድ ቤት በወንጀልና በፍትሐብሄር ክስ እንደሚመሰርቱም አስታውቀዋል፡፡  የፌደራል ፣ የክልል፣ የወረዳ እና የፖሊስ አዛዦችም እንደሚከሰሱ ገልጸዋል።

No comments:

Post a Comment