Friday, February 22, 2013

አባት እና አባቶች፤ ከንብ እና ከንብ abetokichaw


እኛ ምርጫን የተለማመድነው በልጅነታችን ነበር።ለሁለት ተቧድነን እግር ኳስ ልንጫወት ስንሻ ሁለት መራጮች የቡድን አባት ተብለው ይሰየሙና የምንረጠው እኛ ተደብቀን ሄደን የምርጫ ምልክታችንን ይዘን እንመጣለን። ከዛም “አባት እና አባቶች” እንላቸዋለን… አቤት፤ ከአንበሳ እና ከነብር…? አንበሳን ያለ አንበሳውን ነብርን የፈለገ ነብሩን ይወስዳል። ሌላው ደግሞ አባትና አባቶች ከቡኒ እና ከረመዲ…? ብሎ ሊጠይቅ ይችላል። (ቡኒ እና ረመዲ የእርግብ ቀለሞችም ስሞችም ሆነው ያገለግላሉ። እንደዛሬ ራሳችን በራሪ ከመሆናችን በፊት ርግቦችን እናረባ ነበር።)
እናልዎ አሁን የሟሟያ ምርጫ ተቃርቧል። እንዳልኩዎት ወዳጄ ሃና መታሰቢያ በቂርቆስ ከክፍለ ከተማ ለምርጫ የሚወዳደሩ እጩዎችን ዝርዝር ፎቶግራፍ አንስታ አሳይታናለች። በዚህ የምርጫ ጣቢያ ወይዘሮ አዜብ መስፍንም ይወዳደራሉ። የእርሳቸው የምርጫ ምልክት ብቻ ሳይሆን የሁሉም ሰዎች የምርጫ ምልክት ንብ ነው።
ስለዚህም ከእኛ ልጅነት እንኳ ያልተሻለ የምርጫ ውድድር ሊደረግ ነው ማለት ነው። አዎ ወደድንም ጠላንም፤ “አባት እና አባቶች… ከንብ እና ከንብ…?” ልንባል ነው። ሁሉም ንቦች ሁሉም ተነዳፊዎች…! ስለዚህ ምርጫው በጣም ከማይናደፍ እና በጣም ከሚናደፍ ነው ማለት ነው…? እንዲህ አይነቱ ምርጫ ምርጫ ለመባል ይበቃልን!? እግዜር ይወቀው ልል ነበር…!? ይህንን መላ ቅጡ የጠፋ ነገርን እግዜር ይወቅ ብሎ ማለት አምላክን መፈታተን ነው!? እናም እዛው የጉዳዩ ባለቤት ይወቅ እንላለን!
እኔ የምለው…
ወዳጆቼ የኢህአዴግ ዋና ስራ ሂደት ባለቤቶች፤ ይቺ ንብ የምርጫ ምልክት በቃ ለዘላለም ሆነች ማለት ነው? አረ ብትቀየር ይሻላል። ሰዉኮ እነዚህ ሰዎች እስከመቼ እየተቀያየሩ ይነድፉናል እያለ ነው!? ታድያ መንግስት እንኳ ባይቀየር የምርጫ ምልክቱ ቢቀያየር አንድ ለውጥ ነውኮ…! እናንተስ መናደፉ እየደክማችሁም እንዴ!? (እየተባልን ነው…!)

No comments:

Post a Comment