Tuesday, March 5, 2013

በጀርመን የተቃውሞ ሰልፍ ተካሄደ


የካቲት ፳፮ (ሃያ ስድስት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም 
ኢሳት ዜና:- እ.ኤ.አ. በማርች 01 ቀን 2013 ዓ.ም. በጀርመን ፍራንክፈርት ከተማ የኢትዮጵያ ህዝብ አርበኞች ግንባር ዘብ በጠራው የተቃውሞ ሠልፍ ላይ ከተለያዩ የጀርመን ከተሞች የተሰባሰቡ ቁጥራቸው ከ400 በላይ የሆኑ ኢትዮጵያውያን፣ትውልደ-ኢትዮጵያውያንና የኢትዮጵያ ወዳጆች የተገኙ ሲሆን ፣  በተለያዩ መፈክሮችና የኢትዮጵያ ሰንደቅ አላማ በማሸብረቅ ጉዞውን ወደ ኢትዮጵያ ቆንስላ ጽ/ቤት አድርጓል።
”የህሊና እስረኞች ይፈቱ!” ፣”የፕሬስ ነጻነት ይከበር!” ”ሃሳብን በነጻነት የመግለፅ መብት ይከበር!” ”ጅሃዳዊ ሐረካት የወያኔ ፈጠራ ነው!” ”የሃይማኖት ነፃነት ይከበር!” ”በአለም ዙሪያ ያሉ የወያኔ ቆንስላ ፅ/ቤቶች የኢትዮጵያን ህዝብ አይወክሉም!” ”የአውሮፓ ህብረት ለአፋኙ የወያኔ አገዛዝ የሚያደርገውን የገንዘብ ድጋፍ ያቁም!”  ”ከአባይ በፊት ሙስናና ዘረኝነት ይገደብ!” የሚሉ መፈክሮች በሰፊው የተደመጡ ሲሆን ከአንድ ሰዓት ተኩል የእግር ጉዞ በኋላ ተሰላፊው  ቆንስላው ጽ/ቤት ፊት ለፊት ሲደርስ በከፍተኛ ጩኸት እና ፉጨት ተቃውሞውን ማሰማት ችሏል።
በመጨረሻም የኢትዮጵያ ህዝብ አርበኞች ግንባር ተወካይ፣የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን አባቶች እና የሙስሊሙ ማህበረሰብ ተወካዮች በአካል ተገኝተው አጠር ያለ ንግግር ያደረጉ ሲሆን የኢትዮጵያ ህዝብ የጋራ ትግል ሸንጎም ከኔዘርላንድ የላከው ደብዳቤ መነበቡን ኢንጂነር ዳዊት ፋንታ የላከው ዘገባ ያመለክታል።

No comments:

Post a Comment