Wednesday, September 17, 2014

የጊፍት ሪል ስቴት ባለቤት ታሰሩ

የጊፍት ሪል ስቴት ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር ባለቤትና ዋና ሥራአስኪያጅ አቶ ገብረየሱስ ኢተጋ በአዲስአበባ ከተማ አስተዳደር የሊዝ ቦርድ ከተፈቀደላቸው መሬት በላይ ይዘው በመገኘታቸው ተጠርጥረው በቁጥጥር ሥር ዋሉ።
giftአቶ ገብረየሱስ በቀድሞ ወረዳ 28 ልዩ ስሙ የካ አባጣፎ ተብሎ በሚታወቅ አካባቢ ከተረከቡት መሬት በተጨማሪ ከ30ሺ ካሬሜትር በላይ ይዘው በመገኘታቸውና እንዲያስረክቡም በተደጋጋሚ ቢጠየቁም ፈቃደኛ ሆነው ባለመገኘታቸው ከትላንት በስቲያ ሰኞ ዕለት በቁጥጥር ሥር ውለው ትላንት ፍ/ቤት መቅረባቸውን ምንጮቻችን ጠቁመዋል።
ምንጮቻችን እንዳመለከቱት የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የሊዝ ቦርድ ለጊፍት ሪል ስቴት በቀድሞ ወረዳ 28 የካ ለገጣፎ አካባቢ የሚገኝ 13 ሄክታር መሬት ቦታ 21 ባለ 3 ፎቅ ኮንዶሚኒየም፣ 81 ቪላ ቤቶች፣ በመጀመሪያ ፌዝ ለመገንባት፣ 20 ኮንዶሚኒየም ሕንጻ እና 130 ቪላ ቤቶች መዝናኛ ሱቆችና ቢዝነስ ሴንተር ያለው ግንባታ በሁለተኛው ፌዝ ለመሥራት በሪል ስቴት መመሪያው መሠረት የሊዝ ዋጋውን ከፍሎ በሊዝ ቦርድ ቃለጉባዔ ቁጥር 4/97 በቀን 2/2/1997 እንዲወስዱ ተወስኗል። ሆኖም ጊፍት ሪል ስቴት የውል ማሻሻያ አድርገናል በማለት የመሬት መጠኑን አሳድጎ በሕገወጥ መንገድ ትርፍ መሬት መያዙን አስተዳደሩ አረጋግጧል። ይህንን ጉዳይ በቀድሞ አስተዳደሩ ከንቲባ አቶ ኩማ ደመቅሳ የሚመራው አስተዳደር ጥቆማ ቀርቦለት የካቲት 17 ቀን 2004 ዓ.ም በቃለ ጉባዔ ቁጥር 18/2004 ባካሄደው መደበኛ ስብሰባ ጊፍት ሪል ስቴት በሕገወጥ መንገድ የወሰደውን መሬት እንዲመልስ ወስኖ ክፍለ ከተማውም በእጁ የሚገኘውንም ካርታ እንዲያመክን ማዘዙን ምንጮቻችን አስታውሰዋል።
ጊፍት ሪል ስቴት በተደጋጋሚ ጉዳዩን አስመልክቶ ያቀረበው አቤቱታ አስተዳደሩ ሊቀበለው አልቻለም። በዚህ መሠረት በአቶ ድሪባ ኩማ የሚመራው አስተዳደር በ24/10/2006 በቁጥር አ.አ/ከጽ/03/7.7/390 በከንቲባ ጽ/ኃላፊ በአቶ አሰግድ ፊርማ በተፈረመ ደብዳቤ የሪልስቴቱ የአቤቱታ ጥያቄ ውድቅ መሆኑ ተገልጾለታል። ይህም ሆኖ ግን ጊፍት ሪል ስቴት ወደመሬት ባንክ እንዲገባ በተወሰነው ይዞታ ላይ ግንባታ በመጀመሩ የአስተዳደሩ ፍትህ ጽ/ቤት ከዓቃቤ ሕግ ጋር በመቀናጀት አቶ ገብረየሱስ ኢተጋ ሰኞ እለት በቁጥጥር ስር እንዲውሉ ከፍ/ቤት የመያዣ ትዕዛዝበማውጣት ግለሰቡን በቁጥጥር ስር በማድረግ ተባባሪዎችንም በመፈለግ ላይ እንደሚገኝ ታውቋል። አቶ ገብረየሱስ ትላንት በአዲስ አበባ ከተማ የካ ምድብ ችሎት ፍ/ቤት ቀርበው ፖሊስ ምርመራውን ለማጣራት የጠየቀውን የሰባት ቀናት ተጨማሪ ጊዜ ቀጠሮ እንደተፈቀደለት ለማወቅ ተችሏል።
ጊፍት ሪል ስቴት በሕገወጥ መንገድ ይዞታል የተባለው ይዞታ በወቅቱ የመሬት ሊዝ ጨረታ ከፍተኛ ዋጋ ሲሰላ ከ200 ሚሊየን ብር በላይ ግምት እንዳለው ምንጫችን ጠቁሟል።
ምንጭ፡ ዛሬ በአዲስ አበባ ታትሞ የወጣው ሰንደቅ ጋዜጣ
http://www.zehabesha.com/amharic/archives/34644

No comments:

Post a Comment