Monday, February 17, 2014

ማየት ማመን ነው በሚል የኢትዮጵያውያንን የስደት ስቃይ የሚያሳይ የፎቶ ኤግዚብሽን እና የቪዲዮ ቅንብር በኖርዌ ኦስሎ ከተማ ተካሄደ



ፌብሩዋሪ 17, 2014
ሄለን ንጉሤ/ኖርዌ/

የዲሞክራሲያዊ ለውጥ በኢትዮጵያ ድጋፍ ድርጅት ኖርዌ የሴቶችና ወጣቶች ክፍል በሐገራችን ኢትዮጵያ የሰዎች የህገወጥ ዝውውርን በተመለከተና ሰዎች ከሃገራቸው ለምን እንደሚሰደዱ እንዲሁም የስደትን አስከፊነት የሚያሳይ የፎቶ ኤግዚብሽንና ቪዲዮ በDiakonhjemmet university college Oslo February 14, 2014 ለኖርዌጅያንና የተለያየ ሐገር ዜግነት ላላቸው ተማሪዎች አቀረቡ።

ይህ የፎቶ ኤግዚብሽን ዋና አላማው በሐገራችን ኢትዮጵያ በወያኔ የአገዛዝ ዘመን የህገወጥ የሰዎች ዝውውር ቁጥሩ በከፍተኛ ደረጃ እየጨመረ በመምጣቱና ዜጎች በሐገራቸው ለመኖር የሚያስችላቸው መልካም አስተዳደር ስለሌለ የሰብአዊ መብት ጥሰቱ ከእለት ወደ እለት እየጨመረ በመምጣቱ ዜጎች የወያኔ አባል ካልሆኑ በስተቀር ተምረው የስራ እድል ስለማያገኙ፤ የመናገርና የመፃፍ መብታቸው በመገደቡ፤ ዜጎች ያለምንም ቅድመ ሁኔት መሬታቸውን እየተነጠቁ ለውጭ ሐገር ባለሃብቶች በመሸጡ ተለዋጭ ነገር ሳያገኙ ለጎዳና ህይወት በመዳረጋቸው፤ በዘራቸው ምንክያት በሚደርስባቸው ተፅኖ እንዲሁም በፖለቲካ አመለካከታቸው በሚደርስባቸው ከፍተኛ እስር፤ ግርፋትና እንግልት ሳቢያ ሐገራቸውን ለቀው ለመሰደድ ይገደዳሉ። ገዢው መንግስት ህጋዊ የሚላቸው ነገር ግን ህጋዊ ያልሆኑ 250 ኤጀንሲዎችን አቋቁሞ ፍቃድ በመስጠት የዜጎች ሽያጭ በስፋት እንዲያከናውኑ እያደረገ ይገኛል። እነኚህ ኤጀንሲ ተብዬዎች በአብዛኛው እድሜያቸው ለስራ ያልደረሱ ህፃናት ልጆችን ሳይቀር በገጠሪቱ የሃገራችን ክፍል የሚገኙ ወገኖቻችንን በመመልመል የራሳቸውን ኪስ ለማደለብ ለሽያጭ ያቀርባሉ።

ሰዎች ከሐገራቸው እንዲሰደዱ ዋናውን ሚና እየተጫወተ ያለው አምባገነኑ የወያኔ መንግስት ሲሆን እነዚህ ስደተኞች በመንገድ ላይ የሰውነት ብልታቸው ከውስጣቸው እየተወሰደ ሲሽጥ፤ በየመንገዱ ሲሞቱ፤ ሴቶች እህቶቻችን ተገደው ሲደፈሩ፤ ሲደበደቡ፤ የፈላ ውሃና ዘይት በላያቸው ሲደፋ፤ ከፎቅ ተወርውረው ሲሞቱ፤ በየኢምባሲው ደጃፍ ሲጎተቱ፤ አእምሮአቸውን ስተው በየጎዳናው እራቁታቸውን እየሄዱ መሳለቂያ ሲሆኑ በየሃገሩ አምባሳደር ተብለው የተወከሉት ግን ምንም አይነት ወገናዊ ስሜት የሌላቸው በመሆኑ ለወከሉት ህዝብ ከለላ መስጠት ሳይችሉ በተቃራኒው ለአረቦቹ ወግነው ሲናገሩ ይታያሉ። ሐገር ውስጥም ለሚደረገው ህገወጥ ዝውውር ገዢው ፓርቲ ትኩረት ሰጥቶ ባለመከታተሉ ወይም እያየ ዝም በማለቱ ሰዎች በኮንቴነር እንደ እቃ እየታጨቁ የብዙዎች ህይወት ማለፉ ይታወቃል። እነኚህ ከላይ የጠቀስናቸው ችግሮች በሙሉ እየተፈፀመብን ያለው በአምባገነኑ የወያኔ መንግስት መሆኑን ለአለም ለማጋለጥ ማየት ማመን ነው በሚል የወገኖቻችንን ስቃይ ከሐገር ሲወጡ ጀምሮ በመንገድና በደረሱበት ቦታ ሁሉ የሚደርስባቸውን ስቃይና እንግልት የሚያሳየውን የፎቶ ኤግዚብሽን እና ቪዲዮ ፕሮግራም ለማቅረብ የወሰነው።

ዝግጅቱ በኖርዌጅያን የሰአት አቆጣጠር ከጠዋቱ 08፤45 በትምህርት ቤቱ መምህር እና በእኛ በኩል በዶ/ር ሙሉአለም አዳም የመክፈቻ  ንግግር ሲሆን፤ በመቀጠል ተማሪዎቹ ፎቶዎቹን እየተዘዋወሩ የተመለከቱ ሲሆን አዘጋጆቹም ስለፎቶዎቹ ማብራሪያ ሰጥተዋል። ከ15 ደቂቃ እረፍት በኋላ የቪዲዮ ፕሮግራም የቀረበ ሲሆን ይህ ቪዲዮ መምህራኑን ጨምሮ ተማሪዎቹን ያስለቀሰ ሲሆን አንዳንዶቹ ለማየት አቅም በማጣታቸው አዳራሹን ለቀው የወጡም ነበሩ ከቪዲዮ በኋላ ተማሪዎቹ የተሰማቸውን ስሜት ሲገልፁ መንግስታችን በዚህ የሰዎች ንግድ ውስጥ መሳተፉ ያሳዘናት መሆኑን አንዲት ተማሪ ገልፃለች። አዘጋጅ ወጣቶችም የኖርዌጂያን መንግስት ለኢትዮጵያ  የሚሰጠውን ገንዘብ ማቆም እንዳለበትና የወያኔ መንግስት የሚያገኘውን የእርዳታ ገንዘብ መሳሪያ ለመግዛት እና ህዝቦችን ለመጨቆን እየተጠቀመበት በመሆኑ በስልጣን ላይ እንዲቆይ እገዛ እያደረጉ በመሆኑ እኛ በሃገራችን ዲሞክራሲያዊ ለውጥ ለማምጣት እና ይህንን ጨቋኝ   አገዛዝ ለመጣል በምናደርገው ትግል እንቅፋት ሆኖ ያስቸገረን በመሆኑ የኖርዌጂያን ሰዎች የሚለግሱት ገንዘባቸው ለምን ተግባር እንደሚውል እንዲያውቁና ተማሪዎቹም መንግስታቸውን እንዲጠይቁ እንዲሁም ለሚያውቋቸው ሁሉ ያዩት እንዲያስረዱላቸው ጠይቀዋል።

በመጨረሻም መምህራኑ ለአዘጋጆቹ ምስጋና አቅርበው ፕሮግራሙ በኖርዌጅያን የሰአት አቆጣጠር 11፡00
ተጠናቋ። እኛም አዘጋጆቹ ለወደፊት ሐገራችን ከአምባገነኖች ነፃ እስከምትወጣ ድረስ የወያኔን ትውልድ የማጥፋት ሴራ በማጋለጥ እስከመጨረሻው እንደምንሰራ ለመግለፅ እወዳለሁ። ዝግጅቱን ለመመልከት እዚህ ይጫኑ። 
        https://www.youtube.com/watch?v=4oEyoA3WrU8

No comments:

Post a Comment