Wednesday, October 8, 2014

ዛሬም ሆነ ነገ ፕሮፌሠር አሥራት ወልደዬስ የተለሙልን ፈለግ የትውልዳችን ቃልኪዳን ይሁን!

ሞረሽ ወገኔ የዐማራ ድርጅት ለምን እና እንዴት ተመሠረተ?
Moreshልክ የዛሬ ፪(ሁለት) ዓመት መስከረም ፳፯ ቀን ፪ሺህ፭ ዓ.ም.፣ ሞረሽ ወገኔ የዐማራ ድርጅት በዋሽንግተን ዲሲ ከተማ ተመሠረተ። ለድርጅቱ መመሥረት ዋና መሠረታዊ ምክንያቱ ኢትዮጵያዊነቱን በምንም ዓይነት ጥርጥር ውስጥ አስገብቶ የማያውቀው ዐማራ የተጋረጠበት የኅልውና መጥፋት አደጋ እንደሆነ አያጠራጥርም። በተለይም ደግሞ የዐማራው ታሪካዊ ጠላቶች በትግሬ-ወያኔ አገዛዝ አሰባሣቢነት ተቧድነው ባለፉት ፵(አርባ) ዓመታት ያደረጉበት የዘር ማጽዳት እና የዘር ማጥፋት ዘመቻ ሲሆን፣ የጥፋቱ እና የግፉ ብዛትም ሆነ ግዝፈት በዮዲት ጉዲት እና በግራኝ አሕመድ የጥፋት ዘመኖች በዐማራው ላይ ከተፈፀሙት ጭፍጨፋዎች ቢበልጥ እንጂ የማያንስ ነው። ስለሆነም ለሞረሽ-ወገኔ መመሥረት ቆስቋሽ የሆነው ምክንያት፣ ከየካቲት እስከ ሰኔ ፪ሺህ፬ ዓ.ም. በደቡብ ኢትዮጵያ ጉራፈርዳ ወረዳ ይኖሩ በነበሩ ከ፸፰(ሰባ ስምንት) ሺህ የሚልቁ የዐማራ ወገኖቻችን ላይ የትግሬ-ወያኔ አገዛዝ ያካሄደው የዘር ማጽዳት ዘመቻ ነበር።
የትግሬ-ወያኔ አገዛዝ ድርጊት በሁሉም የዓለም ክፍሎች ተበትነው በሚኖሩ የዐማራ ነገድ ተወላጅ ኢትዮጵያውያን ላይ ከፍተኛ የሆነ የመጠቃት ስሜትን መጫሩ እይታበልም። በመሆኑም ናዚያዊው አገዛዝ በሥልጣን ላይ ከተቆናጠጠበት ጊዜ ጀምሮ በዐማራው ነገድ ተወላጅ ኢትዮጵያውያን ላይ የሚያካሂደውን የዘር ማጽዳት እና የዘር ማጥፋት ዘመቻ ለማስቆም፣ የዐማራው ልጆች ያላቸው ብቸኛው አማራጭ መንገድ ተደራጅቶ መታገል መሆኑን ከዘገየም በኋላ ለመገንዘብ በቅተዋል። ይህንን ነባራዊ ሁኔታ የተገነዘቡ እና ለችግሩም ተግባራዊ ምላሽ ለመስጠት ቁርጠኛ የሆኑ፣ በዓለም ዙሪያ የሚኖሩ ከሠላሣ የማይበልጡ የዐማራው ልጆች ከያሉበት ተጠራርተው አንድ ለዐማራው መብት መጠበቅ የሚታገል ድርጅት ማቋቋም ስለሚቻልበት መንገድ መምከር ያዙ። በምክር ብቻ አልተገቱም፤ ከ፭(አምሥት) ወራት ያላሠለሰ ጥረት በኋላ በመስከረም ፳፮ እና ፳፯ ቀን ፪ሺህ፭ ዓ.ም. መሥራች ጉባኤ አካሂደው በጉባኤያቸው ማብቂያ ለዐማራው ኅልውና መጠበቅ ቋሚ ጠበቃ የሆነ ድርጅት መመሥረታቸውን ለዓለም ይፋ አደረጉ። ለድርጅቱም መጠሪያ ዐማራው ለችግር ጊዜ «የድረሱልኝ» ጥሪ ማሠሚያ ባደረገው ቃል «ሞረሽ» የሚል ቅፅል እንዲጨመርበት ሙሉ ስምምነት ላይ ደረሱ። እነሆ ዛሬ ሞረሽ ወገኔ የዐማራ ድርጅት ፪(ሁለት) ዓመት ያስቆጠረ በሁለት እግሩ የቆመ ጨቅላ ለመሆን በቅቷል።
በኢትዮጵያ በ፲፱፻፶ዎቹ(1950ዎቹ) ከተጠነሰሰው የተማሪዎች የለውጥ እንቅስቃሴ ጀምሮ አንድ በሕግ መልክ ተረቅቆ ያልወጣ፣ ግን ዐማራው በዐማራነቱ ተደራጅቶ ለነገዱ እና ለአገሩ ለኢትዮጵያም ዘላቂ ኅልውና መጠበቅ እንዳይታገል ታሪካዊ ጠላቶቹ የሸበቡበት የተንኮል አሽክላ ነበር። እርሱም «ዐማራው በኢትዮጵያዊነቱ ብቻ እንጂ በዐማራነቱ አይደራጅም።» የሚል አጉል ሽንገላን ያዘለ ክፉ የማደንዘዣ አዚም። የሞረሽ-ወገኔ የዐማራ ድርጅት መመሥረት በ፲፱፻፹፬ ዓ.ም. በታላቁ የሕክምና ባለሙያ ፕሮፌሠር አሥራት ወልደየስ ኢትዮጵያ ውስጥ የመላው ዐማራ ሕዝብ ድርጅት (መዐሕድ) ከተቋቋመ ወዲህ በውጭ አገሮች የሚኖሩ ዐማራ ኢትዮጵያውያን ለነገዳቸው እና ለአገራቸው ኅልውና መጠበቅ ሲሉ ያከናወኑት ትልቅ የዕመርታ እርምጃ ሆኖ ሊወሰድ ይችላል።
ድርጅቱ ኅልውናውን ከተቀዳጀ በኋላ ምን፣ ምን ተግባሮችን አከናወነ?
ሞረሽ-ወገኔ ተመሥርቶ በይፋ እንቅስቃሴውን ማካሄድ ከጀመረበት ከመስከረም ፳፯ ቀን ፪ሺህ፭ ዓ.ም. ጀምሮ ቀዳሚ ተግባሩ አድርጎ የወሰደው፣ በሁሉም የዓለም ክፍሎች ተበትነው የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ዐማሮችን ማንቃት እና በድርጅቱ ጥላ ሥር ማደራጀትን ነው። ድርጅቱ በዓለም ዙሪያ ያሉ ዐማሮችን ለመቀስቀስ ከ፷(ስድሳ) የማያንሱ ወቅታዊ መግለጫዎችን፣ በጥናት ላይ የተመሠረቱ ታሪካዊ ዳራ ያላቸው ጽሑፎችን፣ እንዲሁም በድምፅ እና በምሥል የታጀቡ ቅንብሮችን፣ የዘመኑን የኢትተርኔት ቴክኖሎጂን ጨምሮ በተገኙት አጋጣሚዎች ሁሉ በመጠቀም አሠራጭቷል። እንዲሁም በሁሉም የዓለማችን ክፍሎች ስለድርጅቱ እንቅስቃሴ የሚያስተዋውቁ ከ፳(ሃያ) የማያንሱ ሕዝባዊ ስብሰባዎችን አካሂዷል። በእንቅስቃሴውም ገና ከጅምሩ መልካም ፍሬን አፍርቶ፣ በሁሉም የዓለማችን አኅጉሮች የሚኖሩ ዐማራ ኢትዮጵያውያንን ለማሰባሰብ እና የድርጅቱን አካሎች ለማቋቋም ተችሏል። በአውሮፓ እና በአውስትራሊያ ከመሠረታዊ እስከ አኅጉር-አቀፍ ቅርንጫፎች ተዋቅረዋል። በካናዳ እና በተባበሩት የአሜሪካ ግዛቶችም ከመሠረታዊ ማኅበር እስከ አገር-አቀፍ ቅርንጫፎች ድረስ ደረጃ ደረጃ የማዋቀር ተግባሩ ቀጥሏል። መደራጀት በራሱ ብቻውን የትግሉ ግብ ባይሆንም ለዐማራው ነገድ ኅልውና፣ ብሎም ለኢትዮጵያ ዘለቄታዊነት መቀጠል ይህ የመጀመሪያው ወሣኝ ተግባር መሆኑ ግን አያወላውልም።
በዚህ አጭር ዕድሜው ሞረሽ-ወገኔ ካከናወናቸው ታላላቅ ብሔራዊ ግዳጅን የሚመለከቱ ተግባሮች አንዱ የታላቁን የኢትዮጵያ ንጉሠ-ነገሥት የዳግማዊ አፄ ምኒልክን ታሪካዊ አስተዋፅዖ በአዲሱ ትውልድ እንዲዘከር ማድረጉ ነው። እንደሚታወቀው ዳግማዊ አፄ ምኒልክ የዘመናዊት ኢትዮጵያ መሥራች አባት፣ የጥቁር ሕዝብ መኩሪያ የሆነው የታሪካዊው የአድዋ ጦርነት ድል አድራጊ መሪ፣ ኢትዮጵያውያን ወገኖቻቸውም ከዘመናዊ ቴክኖሎጂ ጋር እንዲተዋወቁ መሠረታዊ በሆነ የለውጥ ሂደት እንዲያልፉ ያደረጉ ብልህ እና ጀግና መሪያችን ነበሩ። ሆኖም «የእሣት ልጅ አመድ» ሆኖ ተከታዩ ትውልድ እንኳን የእርሣቸውን የአገር ግንባታ ትልም ሊከተል ቀርቶ ባንዶች እና የባንዳ ልጆች የኢትዮጵያን ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ማኅበራዊ ሕይወት እስከመምራት ደርሰዋል። እኒያ የአድዋን ድል ያስገኙ ጀግኖች አያቶቻችን እና ቅድመ-አያቶቻችን ዛሬ በሕይዎት ኖረው ቢሆን ኖሮ ምን ይሉ ይሆን? ስለዚህም ከታሪክ እና ከትውልድ ተወቃሽነት ለመዳን፣ ሞረሽ-ወገኔ የኢትዮጵያን የረዥም ዘመን ታሪክ ሣያዛባ በኢትዮጵያውያን ሁሉ እንዲዘከር ጥረቱን አጠናክሮ ይቀጥላል።
ሞረሽ-ወገኔ ለወደፊት ምን ዓይነት ተልዕኮዎችን ለመወጣት ተሠናድቷል?
ከከ፵(አርባ) ዓመታት በፊት በመላ ኢትዮጵያ በዐማራው ላይ የታወጀው የዕልቂት ዘመቻ፣ ከዘመን ዘመን እየተሸጋገረ ዛሬ ያለንበት እጅግ አስከፊው ደረጃ ላይ ደርሷል። በተለይም የትግሬ-ወያኔ ናዚያዊ ቡድን በ፲፱፻፸፪ ዓ.ም. በወልቃይት-ጠገዴ በሚኖሩ ዐማራ ኢትዮጵያውያን የጀመረውን የዘር ማጥፋት እና የዘር ማፅዳት ዘመቻ አስፋፍቶ በአሁኑ ወቅት በሁሉም የአገሪቱ ማዕዘኖች በሚኖሩ ዐማሮች ላይ አዳርሶታል። ሰሞኑንም በጋምቤላ ክልል፣ መዠንግር ዞን፣ በሜጢ ከተማ እና በአካባቢው በዐማራ ነገድ ተወላጅ ኢትዮጵያውያን ላይ የሚፈፀመው ድርጊት የዚያው የመጀመሪያው የትግሬ-ወያኔ ፖሊሲ ውጤት መሆኑ አያጠያይቅም። ስለዚህ ዐማራው ዘለቄታዊ ኅልውናውን ለማስጠበቅ ምን ማድረግ አለበት?
በመጀመሪያ የችግሩን መኖር መቀበል ይገባል፥ ኢትዮጵያውያን ዐማሮች የዘር ማፅዳት እና የዘር ማጥፋት ዘመቻ ተከፍቶብን እያለቅን ነው።
ተከታታዩ እርምጃ፥ መደራጀት፣ መደራጀት፣ መደራጀት። በምን መልክ? ዐማራው ኢትዮጵያዊነቱን ሣይለቅ በዐማራነቱ መደራጀት አለበት። ሞረሽ-ወገኔም ዘወትር ጥሪውን የሚያቀርበው ዐማራው በዙሪያው እንዲደራጅ ነው።
ትግል ካሉበት አካባቢ ይጀምራል። በተለይ በስደት የሚኖረው ዐማራ በሚኖርበት አካባቢ የሚገኙ አብያተ-ክርስቲያን፣ መስጊዶችን፣ የኢትዮጵያውያን የሆኑ የተለያዩ የማኅበረሰብ ተቋሞችን እና ድርጅቶች በግዴለሽነት ወይም በቸልተኝነት ለትግሬ-ወያኔዎች እና ለሌሎች ፀረ-ኢትዮጵያ ኃይሎች እያስረከበ፤ በተቃራኒው ግን የኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያውያን መሠረታዊ ጠላት በሆነው «በሻቢያ ጥላ ከለላነት ወያኔን በትጥቅ ትግል ተፋልመን ኢትዮጵያን ነፃ እናወጣለን» ከሚለው የጅሎች የቀን ቅዠት ሊነቃ ይገባዋል። ስለሆነም በመጀመሪያ የዕምነት ተቋሞቹን ማስከበር፤ የማኅበረሰብ መሰባሰቢያ መድረኮችን ከሻቢያ፣ ከትግሬ-ወያኔ እና ከመሠል ፀረ-ኢትዮጵያ ኃይሎች መንጋጋ የማላቀቅ ኃላፊነቱ የእርሱው መሆኑን ተገንዝቦ ለተግባራዊ ምላሽ መንቀሳቀስ ይገባዋል። ከዚያ ወደሚቀጥለው የተግባር ምዕራፍ መሸጋገር ይቻላል።
በአገሩ በኢትዮጵያ የዜግነት መብቱን ነፍገው፣ ፍትኅ አሳጥተው፣ ለአስከፊው እና መራሩ የስደት ሕይዎት የዳረጉት የትግሬ-ወያኔ ቀንደኛ ባለሥልጣኖች፣ በውጪ አገሮች እንደርሱው ስደተኛ መስለው መጥተው አፉን ሊሸብቡት አይገባም። ባለፉት ፳፫(ሃያ ሦሥት) ዓመታት አያሌ የትግሬ-ወያኔ ቀንደኛ ነፍሰገዳዮች ወደውጪ አገሮች በ«ስደት» ስም ወጥተዋል። ሆኖም በኢትዮጵያውያን ላይ ለፈፀሟቸው ኢሰብአዊ ግፎች አንዳቸውም እንኳን በፍርድ ችሎት ቀርበው አያውቁም። ይህ ሁኔታ ሊያበቃ ይገባዋል።
ለማጠቃለል፥ ዐማራ ኢትዮጵያውያን ወገኖቻችን፦ አባቶቻችን፣ እናቶቻችን፣ አያቶቻችን፣ ቅድመ-አያቶቻችንም ሆነ የቀደሙት ኢትዮጵያውያን ወገኖቻችን ነፃነታቸውን አስከብረው፣ ሙሉ አገር ያስረከቡን ከማንም ባገኙት ችሮታ አይደለም። ስለዚህ በዐማራነታችን ተደራጅተን የነገዳችንን ዘለቄታዊ ኅልውና እናስከብር፤ ይህንንም በማድረግ የውዲቷን አገራችንን የኢትዮጵያን ዳግም ትንሣኤ እናፋጥን።

ዐማራን ከፈፅሞ ጥፋት እንታደጋለን!
ፈለገ-አሥራት የትውልዳችን ቃልኪዳን ነው!
ኢትዮጵያ በቆራጥ እና ታማኝ ልጆቿ መስዋዕትነት ለዘለዓለም ታፍራና ተከብራ ትኖራለች!
http://www.zehabesha.com/amharic/archives/35200

No comments:

Post a Comment