Thursday, November 27, 2014

130 የግል ትምህርት ቤቶች ክስ ተመሰረተባቸው

በአዲስአበባ ከተማ የተጋነነ የትምህርት ቤት ክፍያ ዋጋ በመጨመር ህብረተሰቡን ለአላስፈላጊ ወጪ ዳርገዋል በተባሉ 130 የግል ትምህርት ቤቶች ላይ ክስ መመስረቱን የአዲስአበባ ትምህርት ቢሮ አስታወቀ፡፡
የንግድ ውድድርና ሸማቾች ጥበቃ ባለስልጣን እና የግል ትምህርት ቤቶች ማህበር በጋራ ያጠኑትና በሐምሌ ወር 2006 ዓ.ም ይፋ የተደረገ አንድ ጥናት እንደሚያሳየው በአዲስአበባ በግል ት/ቤቶች የአንድ ተማሪ ክፍያ በዓመት እስከ 18ሺ ብር ይደርሳል፡፡
ባለስልጣኑ ከትምህርት ቤቶች ባለቤቶችና አመራሮች ጋር ተከታታይ ውይይት ቢያደርግም አብዛኛዎቹ ያደረጉትን ጭማሪ ለማስተካከል ፍቃደኛ ሳይሆኑ መቅረታቸውን ጠቅሶ በዚሁ መሠረት ከአዲስአበባ የትምህርት ቢሮ ጋር በመተባበር በንግድ ውድድር ሸማቾች ጥበቃ አዋጅ ቁጥር 813/2006 መሠረት በ 130 ያህል ትምህርት ቤቶች ላይ ከሳምንት በፊት ክስ መመስረቱን አስታውቋል።
ትምህርት ቤቶቹ ክስ የቀረበባቸው በነጻ ገበያ ስም ወላጆችን ያላሳተፈ የዋጋ ጭማሪ ባደረጉ፣ በራሳቸው ፍቃድ መጻሕፍትን በማሳተም በከፍተኛ ዋጋ በመሸጥ አርቴፊሻል የዋጋ ንረት እንዲፈጠር ምክንያት ሆነዋል በተባሉ 130 የትምህርት ተቋማት ላይ መሆኑ ተጠቅሷል፡፡ ክሱ የተመሠረተባቸው የትምህርት ተቋማት አብዛኛዎቹ ከአጸደ ሕጻናት እስከ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት የሚሰጡ መሆናቸውን ከአዲስአበባ የትምህርት ቢሮ የተገኘ መረጃ ይጠቁማል፡፡
በአዲስአበባ ከተማ በጠቅላላው 1ሺ 671 የግል የትምህርት ተቋማት ይገኛሉ።
የንግድ ውድድርና ሸማቾች ጥበቃ ባለስልጣን እና የግል ትምህርት ቤቶች ማህበር በጋራ ያስጠኑት ጥናት
እንደሚያሳየው በ2007 ዓ.ም የሚታየው የክፍያ መጠን ከ2005 ዓ.ም ጋር ሲነጻጸር እጅግ ከፍተኛ ጭማሪ
አሳይቷል፡፡ በጥናቱ መሠረት በአዲስአበባ በግል ት/ቤቶች የሚማር አንድ ልጅ ዝቅተኛ ክፍያ በዓመት 3ሺ
250 ሲሆን ከፍተኛው ደግሞ 18ሺ ብር ነው፡፡ ጥናቱ እንዳለው አንድ ወላጅ በአማካይ በዓመት ለአንድ ልጁ 7ሺ 892 ብር ይከፍላል፡፡ የትምህርት ቤቶቹ ዓመታዊ የዋጋ ጭማሪም በየዓመቱ ከ300 እስከ
1ሺ 200 ብር የሚደርስና እጅግ የተጋነነ መሆኑም በጥናቱ ተመልክቷል፡፡
የትምህርት ተቋማቱ በዋነኝነት በቂ የትምህርት ዝግጅትና ልምድ ያላቸው መምህራን ክፍያ በከፍተኛ ሁኔታ በማሻቀቡ እንዲሁም በሌሎች የትምህርት ግብዓቶች ዋጋ መጨመር ምክንያት ወጪያቸውን ለመሸፈነን ሲሉ ዋጋ እንደሚጨምሩ ገልጸዋል፡፡አንድ ስማቸውን መግለጽ ያልፈለጉ የአንድ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ርእሰ መምህር ለዘጋቢያችን እንደተናገሩት ትምህርት እንደማንኛውም ሸቀጥ ቢዝነስ መሆኑንና ከሌሎች አቻ ተቋማት ጋር ውድድር ያለበት ስራ መሆኑን ጠቅሰው ይህን ሥራ በጥራት ለማከናወን ከፍተኛ ወጪን እንደሚጠይቅ እና ወጪውም ከተማሪዎች ክፍያ ተሰብስቦ የሚሸፈን መሆኑን አስረድተዋል፡፡
በነጻ ገበያ መርህ ውስጥም መንግስት ጣልቃ ገብቶ ዋጋ ቀንስ፣ ጨምር የሚልበት አግባብ ሕገወጥ መሆኑን ያስረዱት እኚሁ ርዕሰ መምህር ነገርግን ዋጋ እንድንወንስ ተገደን እምቢ በማለታችን መከሰሳችንን በመገናኛ ብዙሃን እየሰማን መሆኑ ያሳዝናል ብለዋል፡፡

No comments:

Post a Comment